የጠቅላይ ሚንስትሩ የምስራቅ አፍሪካ ጉዳዮች አማካሪ ሚኒስትር አቶ ጌታቸው ረዳ በአዲሱ የትግራይ ጊዚያዊ አስተዳደር ፕሬዜዳንት ታደሰ ወረደ (ሌ/ጀነራል) የቀረበላቸው የክብርና የምስጋና የሽኝት መድረክ ውድቅ አደረጉ።
አቶ ጌታቸው ረዳ ሚያዝያ 3/2017 ዓ.ም የጠቅላይ ሚንስትሩ የምስራቅ አፍሪካ ጉዳዮች አማካሪ ሚኒስትር ሆነው ከተሾሙ በኃላ ለመጀመሪያ ጊዜ ለሚድያ ቃለ-መጠይቅ ሰጥተዋል።
ሚንስትሩ UMD ለተባለ ሚድያ በትግርኛ ቋንቋ በሰጡት ቃለመጠይቅ ” በትግራይ የተደረገው የስልጣን ሽግግር የትግራይ ህዝብን ደህንነትና ህልውና የሚያስጠብቅ አይደለም ” ብለውታል።
የኢፌዴሪ ጠቅላይ ሚንስትር ለደህንነታቸው ያደረጉትን ጥንቃቄ እውቅና በመስጠት ያመሰገኑት አቶ ጌታቸው ፤ በማንኛውም መመዘኛ የትግራይ ህዝብ መልሶ ወደ ጦርነት እንዳይገባ የቻሉትን ሁሉ እንደሚያደርጉ ቃል ገብተዋል።
የፕሪቶሪያ የሰላም ስምምነት ከጫፍ እንዲደርስ አበክረው እንደሚሰሩ ገልጸው ‘” በትግራይ የተጀመረው የለውጥ ፍላጎት ወደ ኋላ የሚጎትት ማንኛውም እንቅስቃሴ ተቀባይነት የለውም ” አይሳካም ብለዋል።
ትግራይ ላይ እሳቸውን ለመግደል የተሸረበ ሴራ እንደነበር ፤ ይህንን ሽሽተው ከትግራይ ፓለቲካ የመውጣት አንዳች ፍላጎት እንደሌላቸው ተናግረዋል።
” የተደረገው የስልጣን ሽግግር ጠቅላይ ሚንስትሩ በተገኙበት በትግራይ መቐለ ቢሆን ትልቅ ትርጉም ይኖረው ነበር ” ያሉት አቶ ጌታቸው ” ትናንትን እየመዘዙ ቁርሾና ቂም በቀል ማቀጣጠል ፋይዳ የለውም ” በማለት ተናግረዋል።
” እኔን በክብር መሸኘት ቅድሚያ የሚሰጠው አይደለም ፤ ቅድሚያ የሚሰጠው በትግራይ የሰፈነው ህግ አልባ አካሄድ እንዲስተካከል መስራት ነው ” ሲሉ አክለዋል።
” የትግራይ ህዝብ የሰጠኝ ክብርና እውቅና ከፍተኛ ነው ፤ ከዚህ ክብርና እውቅና በላይ የምመኘው የምስጋና መድረክ የለም ” ሲሉ የገለፁ ሲሆን በአዲሱ ፕሬዜዳንት የቀረበላቸው የምስጋናና የክብር የሸኝት መድረክ እንደማይቀበሉት አሳውቀዋል።
በክልሉ ያሉ ሌቦችና ህገ-ወጦች አደብ ለማስገዛት ለሚደረገው ጥረት እንደሚያግዙ ህዝቡ ለማገለገል እንደ ትናንት ዛሬም ዝግጁ እንደሆኑም ገልጸዋል።