#Ethiopia | ቻይና እአአ በ2030 በአየር እየበረሩ ከተሞቸን የሚያገናኙ ከአንድ መቶ ሺህ በላይ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎችን በማምረት ገበያውን ለመቆጣጠር እየሰራች ነው፡፡
ይህ ሌላኛው የኢኮኖሚ ከፍታዋ መነሻ እንደሆነ የገለጸችው ቻይና፣ የዚህ ስራ ግብ የከተሞች ትራንስፖርት አገልግሎትን በአየር ታክሲዎች ፣ በጭነት ድሮኖች እና በኤሌክትሪክ በሚሰሩ የአየር ላይ ተሽከርካሪዎች መሰረታዊ እመርታ ማምጣት እንደሆነ አስታውቃለች፡፡
አውቶ ፍላይት እና ኢ ሀንግ የመሳሰሉ ኩባንያዎቸ በጃፓን የሙከራ በረራ በማድረግ የተሳካላቸው ሲሆን ይህንን ሙከራ በደቡብ ምስራቅ እስያ እና በመካከለኛው ምስራቅ ለማስፋፋትም ትልቅ እንቅስቃሴ ተጀምሯል፡፡
የቻይና ደቡባዊ የቴክኖሎጂ ማዕከል ሼንዘን ከተማ በበረራ ታክሲዎች እና በአውሮፕላን ማጓጓዣ ዘርፍ ግንባር ቀደም ለመሆን በማለም በሚቀጥሉት ሁለት ዓመታት ውስጥ ዘርፉን ለማስፋፋት 12 ቢሊዮን ዩዋን (1.7 ቢሊዮን ዶላር) ለመሠረተ ልማት ግንባታ ለማፍሰስ ቃል ገብታለች ።
ሼንዘን በ2026 ከ1,200 በላይ የማኮብኮቢያና የማረፊያ ስፍራዎችን ለመገንባት ዕቅድ የያዘች ሲሆን ለዚህም በበረራ ወቅት የሚኖረውን የአየር ትራፊክ የኔት ወርክ፣ የሎጂስቲክስ እና አስተዳደራዊ ጉዳዮች ስራ ለማቀላጠፍ እየሰራች ትገኛለች፡፡
ሼንዘን በያዝነው አመት አጋማሽ ላይ 249 የማኮብኮቢያ እና የማረፊያ ሜዳዎችን የገነባች ሲሆን በዚህ አመት መጨረሻ 147 ተጨማሪ ግንባታዎችን ለማከናወን አቅዳለች፡፡
የከተማው የትራንስፖርት ቢሮ እንዳስታወቀው በ 2025 ሌሎች 658 መገልገያዎችን ለማጠናቀቅ አቅዳ እየሰራች ነው፡፡