#Ethiopia | በውድነህ ክፍሌ ተደርሶ በተስፋዬ ገ/ሐና የተዘጋጀውና በበርካቶች ዘንድ ተወዳጅ የሆነው “ባቢሎን በሳሎን” ተውኔት ከሁለት ዓመት በኃላ ለአጭር ጊዜ ወደ መድረክ ሊመለስ እንደሆነ አርትስ ስፔሻል ከደራሲው ያገኘው መረጃ ያመለክታል።
“ባቢሎን በሳሎን” ተውኔትን በአውሮፓ ለሁለተኛ ጊዜ ለማሳየት እንቅስቃሴዎች እንደተጀመሩ የተገለፀ ሲሆን ተውኔቱ ወደ አውሮፓ ከመጓዙ በፊት ለአጭር ጊዜ በዓለም ሲኒማ እንዲታይ ከሲኒማ ቤቱ አስተዳደር ጋር ንግግር እንደተጀመረ እና በቅርቡ በድጋሚ ለመድረክ እንደሚበቃ ውድነህ ክፍሌ ለአርትስ ስፔሻል ተናግሯል።
ተውኔቱ ወደ መድረክ መቼ ይመለሳል የሚለው ጥያቄ የበርካታ ቴአትር አፍቃሪን ጥያቄ እንደሆነ የገለፀው ደራሲው “ባቢሎን በሳሎን” ወደ መድረክ እንዲመለስ “የዓለም ሲኒማ ኃላፊዎችም ያሻነውን ቀን እንደሚሰጡን ቃል ገብተውልናል” ብሏል።
“ባቢሎን በሳሎን” ተውኔት ወደ መድረክ ሲመለስ አርቲስት አለማየሁ ታደሰን ጨምሮ ሁሉም ተዋናዮች እንደሚኖሩም ተገልጿል።
ለ22 ዓመታት በኢትዮጵያ ብሔራዊ ቴአትር መድረክ ላይ ሲቀረብ የቆየው “ባቢሎን በሳሎን” ተውኔት ከሁለት ዓመት በፊት ከመድረክ መሰናቱ ይታወሳል።